Quantcast
Channel: Articles
Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

‘እንዳልተሰጠ የሚቆጠር ውሳኔ’ ምን ዓይነት ነው?

$
0
0

በህግ አግባብ የተቋቋመ ፍርድ ቤት ግራ ቀኙን አከራክሮ ውሳኔ ከሰጠ በኋላ ለአፈጻጸም ሲቀርብ ውሳኔው እንዳልተሰጠ ተቆጥሮ አፈጻጸሙን በያዘው ፍርድ ቤት ዋጋ የሚያጣበት የህግ መሰረት አለ? ከሰበር ችሎት ውሳኔዎች ለመረዳት እንደሚቻለው አንድ ውሳኔ በሶስት መንገዶት እንዳልተሰጠ ሊቆጠር ይችላል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱ የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን አለመኖር ነው፡፡ ምንም እንኳን ችሎቱ በአንድ መዝገብ ላይ ይህን አቋም ቢያራምድም በሌሎች ሁለት መዝገቦች ላይ ግን ራሱን በመቃረን የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን የፍርድ ቤትን ውሳኔ እንዳልተሰጠ እንደማያስቆጥረው የህግ ትርጉም ሰጥቷል፡፡ ሌሎቹ ሁለት መንገዶችና የችሎቱ ተቃርኖ የታየባቸው መዝገቦች የሚከተሉት ናቸው፡፡

  1. የሥረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በሌለው ፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ

አንድ ፍርድ ቤት ጉዳዩን ከማየቱ በፊት የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ያለበት ሲሆን የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በተከራካሪ ወገኖች ባይነሳም በማናቸውም የክርክር ደረጃ ፍርድ ቤቱ በራሱ ሊያነሳው የሚገባው ጉዳይ መሆኑ ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 9 እና 231/1/ ሰ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዲይ ነው፡፡ የሥረ ነገር የዳኝነት ስልጣን በሌለው ፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ደግሞ በመርህ ደረጃ እንዳልተሰጠ የሚቆጠር ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 64703 ቅጽ 12፣[1] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 9፣ 231/1/ ሰ

  1. ችሎት ለማስቻል በህጉ የተቀመጠው የዳኞች ቁጥር ባልተሟላበት ሁኔታ የሚሰጥ ውሳኔ

ጉዳዮች በሥነ ሥርዓት ሕጉ መሠረት የሚመሩበት አይነተኛ አላማ ክርክሮችን ፍትሃዊ በሆነ እና ሥርዓት ባለው መንገድ በመምራት በአጭር ጊዜ እና በአነስተኛ ወጭ እንዲቋጩ ማድረግ ስለመሆኑ ይታመናል፡፡ ይህንኑ የሥነ ሥርዓት ሕጉን አላማ ለማሳካት ደግሞ በሕጉ የተመለከቱትን የስነ ሥርዓት ድንጋጌዎችን እንደየአግባብነታቸው መከተልን የግድ ይላል፡፡ በስነ ሥርዓት ሕጉ የተመለከቱት ድንጋጌዎችን እንደየአግባብነታቸው ያለመከተል በተከራካሪ ወገኖች መሰረታዊ መብት ላይ አሉታዊ ውጤት ማስከተሉ አይቀሬ ነው፡፡ ስለሆነም በስነ ስርዓት ሕጉ የተመለከቱት ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት ሊኖራቸው የሚገባው ለጉዳዩ አግባብነት ሲኖራቸው እንጂ በዘፈቀደ ሊሆን አይገባም፡፡

ድንጋጌዎቹ አግባብነት ያላቸው ስለመሆኑ ከመለየቱ በተጨማሪ በጉዳዩ ላይ ተገቢነት አለው የሚለውን ትዕዛዝ ወይም ውሣኔ የሚሰጠው ችሎትም በሕጉ አግባብ የተመለከተው የዳኞች ቁጥር የተሟላ ሊሆን ይገባል፡፡ በሕጉ አግባብ ሊሟላ የሚገባው የዳኞች ቁጥር ሳይሟላ የሚሰጠው ትእዛዝ ወይም ውሣኔ እንደተሰጠ የማይቆጠርና ሕጋዊ ውጤት ሊኖረው የሚገባ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ 73696 ቅጽ 13[2]

  1. በሞተ ሰው ውክልና ክርክር ተደርጎ የተሰጠ ውሳኔ

በሞተ ሰው ስም ቀደም ብሎ የተሰጠን ውክልና በመያዝ የሚቀርብ ክስ፣ የሚደረግ ክርክር እና የሚሰጥ ውሣኔ ህጋዊ ዕውቅናና ውጤት ሊሰጠው የማይገባው ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 95587 ቅጽ 17፣[3] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 57፣ ፍ/ህ/ቁ. 2232/1/

ከሰ/መ/ቁ. 64703 ጋር ተቃርኖ

አንድ ፍርድ ቤት የሰጠው ውሣኔ በሕግ ከተሰጠው የስረ ነገር የዳኝነት ስልጣን ውጭ የሆነ ጉዳይ በማየት የሰጠው ቢሆንም፣ ይህ ውሣኔ በይግባኝ ታይቶ እንዲታረም ካልተደረገ በስተቀር በፍ/ሥ/ሥ/ሕግ ቁጥር 212 በጉዳዩ ላይ አስገዳጅነት ያለውና የመጨረሻ ውሣኔ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 85718 ቅጽ 15[4]

በሕግ አግባብ በፍ/ቤት የተሰጠን ውሣኔ የሞራልን ወይም የሕሊናን አስተሳሰብ መሠረት በማድረግ ዋጋ አልባ ሆኖ እንዲቀር ማድረግ በየትኛውም መለኪያ ተቀባይነት የሚኖረው አይደለም፡፡

ሰበር መ/ቁ. 38041 ቅጽ 8[5]

[1] አመልካች ሻምበል ለታይ ገ/መስቀል እና ተጠሪ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የወረዳ 1 አስተዳደር ጽ/ቤት ሐምሌ 29 ቀን 2003 ዓ.ም.

[2] አመልካች ወ/ሪት ሃና አበባው እና ተጠሪ አቶ አብዱ ይመር /በሌለበት/ ሚያዝያ 9 ቀን 2004 ዓ.ም.

[3] አመልካች ወ/ሮ ሐዋ በከር እና ተጠሪ እነ አቶ ቶፊቅ መሀመድ 2 ሰዎች ጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

[4] አመልካች አቶ ቴዎድሮስ አማረ እና ተጠሪ አቶ አዲሱ ፍሰሃ ሰኔ 03 ቀን 2005 ዓ.ም.

[5] አመልካች ታደሰ ገ/መስቀል ተጠሪዎች እነ ሙሉጌታ ዘካርያስ /7 ሰዎች/ መጋቢት 22 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

Trending Articles