Quantcast
Channel: Articles
Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

ይርጋ፡ ማንሳት መተው መቋረጥ እና መነሻ ጊዜ

$
0
0

ይርጋ

በህግ ተለይቶ ከተቀመጠው የጊዜ ገደብ በኋላ በአንድ ጉዳይ ክስ ለማቅረብ የሚከለከልበት የህግ ፅንሰ-ሃሳብ

ይርጋ አንድ ሰው በጉዳዩ ላይ መብት ያለው ቢሆንም እንኳን ይህንን መብቱን ለመጠየቅ የማይችልበትን ገደብ የሚመለከት ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 44800 ቅጽ 10[1]

የይርጋ ህግ መሰረታዊ አላማ ተገቢውን ጥረት የሚያደርጉ ገንዘብ ጠያቂዎችን ወይም መብት አስከባሪዎችን መቅጣት ሳይሆን መብታቸውን በተገቢው ጊዜ ለመጠየቅ ጥረት የማያደርጉትን ሰዎች መቅጣት መሆኑ ይታመናል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 98358 ቅጽ 17[2]

የይርጋ መቃወሚያ ማንሳት

ክሱ በይርጋ ቀሪ እንደሚሆን በመግለጽ የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ /በተከሳሽ/ ማቅረብ

የይርጋ ደንብ ተፈጻሚ የሚሆነው ክስ ከቀረበ በኋላ ተከሳሹ የይርጋ መቃወሚያ አንስቶ የተከራከረ ከሆነ ነው፡፡ ከሳሽ ክስ የማቅረብ መብቱ በይርጋ ቀሪ ከሆነ በኋላ ክስ አቅርቦ ተከሳሽ ክሱ በይርጋ ቀሪ መሆኑን በመግለጽ ካልተቃወመ ክሱ ተቀባይነት አግኝቶ መታየት ይቀጥላል፡፡ የጊዜ ገደቡ በማለፉ ብቻ ፍ/ቤት ይርጋውን በራሱ አነሳሽነት አንስቶ ክሱን ውድቅ ሊያደርግ አይችልም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 44800 ቅጽ 10[3]

በመርህ ደረጃ የይርጋ ጥያቄ በተከራካሪዎች ካልተነሳ ፍርድ ቤቱ በራሱ አነሳሽነት ሊያነሳው አይችልም፡፡ የይርጋን ጉዳይ የማንሳት ወይም ያለማንሳት ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ የተከሳሽ ወገን ነው፡፡ ይህ አጠቃላይ መሰረተ ሀሳብ ግን ባልተነጣጠለ ኃላፊነት በተከሰሱ ተከሳሾች ላይ ተፈጻሚነት የለውም፡፡ በዚህን ጊዜ በአንደኛው ተከሳሽ የሚነሳ የይርጋ መቃወሚያ ክሱን በይርጋ ቀሪ የሚያደርገው ቢሆን መቃወሚያው በሁሉም ተከሳሾች እንደተነሳ ተቆጥሮ ክሱ ውድቅ መደረግ ይኖርበታል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 19081 ቅጽ 4፣[4] ፍ/ህ/ቁ. 1677፣ 1901

ተከራካሪዎች የይርጋ ጥያቄ እስካቀረቡ ድረስ ጥያቄውን በትክክለኛው አንቀጽ መሰረት እንዲመራ ማድረጉ የፍርድ ቤት ሃላፊነት ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 17937 ቅጽ 4፣[5] ፍ/ህ/ቁ. 1000፣ 1677፣ 1845

የይርጋ ደንብ አንድ ክስ በፍርድ ቤት ቀርቦ በስረነገር እንዳይታይ የሚከለክል ሲሆን የሕሊና ግምት (በ2024 የሰፈረው የመክፈል ግምትን ጨምሮ) በሌላ በኩል የማስረዳት ሸክምን ከአንድ ወገን ወደ ሌላው የማስተላለፍ ውጤት ብቻ ያለው በመሆኑ ከሣሽ ያቀረበውን ክስ ይዘት መርምሮ ውሣኔ መስጠትን የሚከለክል አይደለም፡፡ በፍትሐብሔር ሕጉ ውስጥ የሰፈረውን ይርጋ ተከሣሹ ወገን ካላነሳው ፍርድ ቤቱ በራሱ ሊያነሳ እንደማይችል በፍትሐብሔር ሕግ ቁ.1856 የተጠቀሰ ቢሆንም ይህ ድንጋጌ ተፈጻሚነት የሚኖረው ለይርጋ ድንጋጌዎች እንጂ በሕግ ግምት የማስረዳት ሸክም ከአንድ ተሟጋች ወደ ሌላው በሚዘዋወርባቸው ሁኔታዎች አይደለም፡፡

በመሆኑም ይርጋን (Period of limitation) ከሕግ ግምት (Presumptions) ጋር በማመሳሰል ለይርጋ ተፈፃሚ የሚሆነው ሕግ ለህግ ግምትም ተፈፃሚ መሆን ይገባዋል በማለት የሚቀርብ ክርክር የህጉን መንፈስ፣ ዓላማና ግልጽ ይዘት ያልተከተለ በመሆኑ ተቀባይነት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 17068 ቅጽ 1[6]

ይርጋ መተው

አንድ ሰው የይርጋ ጊዜውን ትቶታል የሚባለው ለዕዳው ምንጭ የሆነውን ግዴታ በማመን አዲስ መተማመኛ ሰነድ የሰጠ እንደሆነ ነው፡፡ ይርጋን መተው ውጤቱ ይርጋን የሚያቋርጥ ሳይሆን አዲስ የይርጋ ጊዜ መቆጠር እንዲጀምር ያደርጋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 90361 ቅጽ 6[7]

ይርጋ መቋረጥ

በፍ/ብ/ሕ/ቁ/1852 ድንጋጌ መሠረት ይርጋ በተቋረጠ ጊዜ ከተቋረጠበት ጊዜ ጀምሮ እንደገና አዲስ የይርጋ ዘመን መቁጠር እንደሚጀምር በዚሁ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር /1/ ሥር ተመልክቷል፡፡ ከዚህ ድንጋጌ በግልጽ መረዳት የሚቻለው ይርጋው በተቋረጠ ጊዜ ቀድሞ የነበረው የይርጋ ጊዜ እንደ አዲስ መቁጠር የሚጀምር መሆኑን ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 31185 ቅጽ 6[8]

በሕግ ተለይቶ የተወሰነ የይርጋ ጊዜ የመቋረጥ እና ያለመቋረጥ ጉዳይ አከራካሪ ነጥብ ሆኖ ሊነሳ የሚችለው የይርጋውን መቆጠር ያቋርጠዋል የተባለው ምክንያት የተከሰተው የይርጋው ጊዜ ከመሙላቱ በፊት በሆነ ጊዜ እንጂ የይርጋው ጊዜ የሞላ ወይም ያለፈ በሆነ ጊዜ ጭምር አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 90361 ቅጽ 6[9]

ክስ የማቅረብ ውጤት

ስልጣን ለሌለው የዳኝነት አካል ክስ ማቅረብ ይርጋን ያቋርጣል፡፡

(በመዝገብ ቁጥር 16648 ስለ ይርጋ ጊዜ አቆጣጠርና ስለ ይርጋ መቋረጥ የተሰጠው የሕግ ትርጉም ተለውጧል፡፡)

ሰ/መ/ቁ. 36730 ቅጽ 9[10]

ክስ የማቅረብ ውጤት /ሽያጭ ውል/

ይርጋ ከሚቋረጥባቸው ምክንያቶች አንደኛው ባለገንዘቡ መብቱ እንዲታወቅለት በፍ/ቤት ክስ አቅርቦ ለባለእዳው አስታውቆ የተገኘ እንደሆነ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43992 ቅጽ 10፣[11] ፍ/ህ/ቁ. 1851(ለ)

ክሱ የቀረበው መብቱን በሚጠይቀው ባለገንዘብ ባይሆንም ባለዕዳው በባለገንዘቡ ላይ ያቀረበው ክስ በይዘቱ የይርጋ መቃወሚያ ከተነሳበት ክስ ጋር ተያያዥነት ካለው ይርጋውን ያቋርጠዋል፡፡

የማይንቀሳቀስ ንብረት ገዢ ንብረቱን ለመረከብ (የሽያጭ ውሉ እንዲፈጸምለት) ያቀረበው ክስ ከሽያጭ ውሉ ቀን ጀምሮ ሲቆጠር በይርጋ የሚቋረጥ ቢሆንም ሻጭ ቀደም ብሎ የሽያጭ ውሉ እንዲፈርስለት ክስ ካቀረበ በገዢው ላይ ተፈጻሚ የሚሆነውን የይርጋ ጊዜ ያቋርጠዋል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 43636 ቅጽ 10[12]

በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1776 እና በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ድንጋጌዎች መሠረት የቤት ሽያጭ ውል ይፈጸምልኝ ክስ ሲቀርብ በሕግ የተደነገገው የይርጋ ሕግ የጊዜ ገደብ አልፏል ወይስ አላለፈም? የሚለውን ነጥብ ለመወሰን በመጀመሪያ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌ ይዘት መንፈስና ዓላማ እንደዚሁም ድንጋጌው ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 መሠረታዊ መርህና ስለ ሽያጭ እና ጠቅላላ ውል ከተደነገጉ ድንጋጌዎች ጋር ሊኖረው የሚገባውን ተፈፃሚነት መመርመር ያስፈልጋል፡፡

  1. የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2893 ንዑስ አንቀጽ 3 “ስለሆነም ሻጭ ውሉን እንደውሉ ቃል ለመፈፀም መዘግየቱን ከተረዳበት ጊዜ አንስቶ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ውሉ እንዲፈፀምለት ካልጠየቀ በቀር ገዢው ውሉ በግዴታ እንዲፈፀም የማድረግ መብቱን ያጣል” በማለት ይደነግጋል፡፡ እዚህ ላይ በአማርኛው “መዘግየቱን ከተረዳበት” በሚለውና በእንግሊዘኛው “ascertained” በሚለው ቃል መካከል ልዩነት ያለመሆኑን ለመገንዘብ እንችላለን፡፡ የድንጋጌው መንፈስ ገዥ በአንድ ዓመት ውስጥ ውሉ እንዲፈፀምለት ለፍርድ ቤት ክስ ማቅረብ ያለበት ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት ለመፈፀም ፈቃደኛ አለመሆኑን ካረጋገጠበት ጊዜ ጀምሮ እንደሆነ የእንግሊዘኛውን የቃል አጠቃቀም በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡

እዚህ ላይ የሚነሣው ጥያቄ ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት ለመፈፀም እንደማይፈልግ ገዥ ያረጋገጠ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ ያለበት ማን ነው? የሚለው ነው፡፡ ለዚህ መሠረታዊ ነጥብ እልባት ለመስጠት ስለውል እና ተዋዋይ ወገኖች በፍትሐብሔር ሕጉ የተቀመጠ የሕግ ግምቶችን ማየት አስፈላጊ ነው፡፡

  1. በሕግ አግባብ የተቋቋሙ ውሎች ባቋቋሟቸው ሰዎች ላይ ሕግ ናቸው በማለት የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1731ንዑስ አንቀጽ 1 የደነገገ ሲሆን ውሎች በተዋዋይ ወገኖች መካከል ሊኖር የሚገባውን የቅንነት የመተማመን ግንኙነት መሠረት በማድረግ በቅን ልቦና ሊተረጎሙ እንደሚገባ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1732 ይደነግጋል፡፡ ከዚህ አንፃር ስናየው ተዋዋይ ወገኖች በተዋዋሉት የውል ቃል መሠት ውሉን የመፈፀም ፍላጎትና ቅን ልቦና ያላቸው መሆኑ የውል ሕግ ግምት የሚወስድበት ጉዳይ በመሆኑ ገዥ ሻጭ በሽያጭ ውሉ በገባው የውል ቃል መሠረት እንደሚፈጽም የተለያዩ የተስፋ ቃሎችን ሲሰጠው የቆየ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ የለበትም፡፡

በተቃራኒው የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌን ጠቅሶ የሚከራከር ሻጭ ከገዥ ጋር ባደረገው የቤት ሽያጭ ውል መሠረት ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ገዥ በማያሻማ ሁኔታ እንዲያውቅ እና እንዲረዳው ያደረገ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ሻጭ በውሉ መሠረት ለመፈፀም እንደማይፈልግ በእርግጠኝነት ገዥ እንዲያውቅ ካደረገው ከአንድ ዓመት በኋላ የሽያጭ ውሉ በፍርድ ኃይል እንዲፈፀምለት የጠየቀ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ ስለሆነም የማይንቀሣቀስ ንብረት የሸጠ ሰው ሻጭ በሽያጭ ውሉ መሠረት የቤቱን ይዞታና የባለቤትነት ሰነዶች ለገዥ ያላስረከበ ከሆነ ውሉን ለመፈፀም ፈቃደኛ አለመሆኑንና በጽሑፍና በማያሻማ ሁኔታ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዠ ካሣወቀው ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ያቀረበ መሆኑን ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡

ሻጭ በውሉ መሠረት የቤቱን ይዞታና የባለቤትነት ሰነዶች ለገዥ አስተላልፎ ከሆነ ገዥ ሻጭ በውሉ መሠረት ይፈጽማል የሚለውን ዕምነት የሚያጠናክርና ውሉም በከፊል መፈፀም መጀመሩን የሚያሣይ መሆኑን ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 እና ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2274 ድንጋጌዎች ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሰለሆነም ሻጭ የቤቱን ባለሀብትነት ለገዥ ለማስተላለፍ እንደማይፈልግና የቤቱን ይዞታ ሻጭ በመልቀቅ እንዲያስረክበው የከፈለውንም ገንዘብ ገዥ እንዲወስድ በማያሻማ ሁኔታ የፍትብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዥ ያሣወቀ መሆኑን ማስረዳት ይጠበቅበታል፡፡

ሻጭ የቤቱን ሰነዶች ለገዥ አስተላልፎ የቤቱን ይዞታ ይዞ በሚገኝበት ጊዜ የቤቱን ሰነዶች ሻጭ እንዲመልስለት የከፈለውን ገንዘብ እንዲወስድ በማያሻማ ሁኔታና የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1789 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው አይነት ለገዥ ያሣወቀ መሆኑን ማስረዳት የሚጠበቅበት ሲሆን ከላይ ከተጠቀሱት ሁኔታዎች በአማራጭ ሻጭ ውሉ እንዲፈርስለት ወይም እንዲሰርዝለት በፍርድ ቤት ክስ አቅርቦ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ገዥ እንዲረዳው ከተደረገ ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ገዥ ያቀረበ መሆኑን ወይም በሕግ እውቅና ላለው የሽምግልና ተቋም ሻጭና ገዥ በነበራቸው ድርድር ሻጭ ውሉን ለመፈፀም እንደማይፈልግ ገዢ  እንዲረዳው ከተደረገ ከአንድ ዓመት በኋላ ክሱን ያቀረበው መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡ በአጠቃላይ ሻጭ በገባው የሽያጭ ውል ቃል መሠረት ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ለገዥ ካሣወቀውና ገዥም ይህንኑ ከተረዳና ካረጋገጠ ከአንድ ዓመት በኋላ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ገዥ ያቀረበ መሆኑን የማስረዳት ግዴታ አለበት፡፡

ሻጭ በውሉ መሠረት ለመፈፀም የማይፈልግ መሆኑን ገዥ ያረጋገጠ መሆኑን ገዥ ውሉ እንዲፈፀምለት ማስጠንቀቂያ መስጠቱንና ማስጠንቀቂያ ከሰጠ በኋላ ሻጭ በውሉ መሠረት አለመፈፀሙን በማየት ብቻ ለማረጋገጥ አይችልም፡፡ ሻጭ ገዥ ማስጠንቀቂያ ከሰጠው በኋላም ቢሆን የተለያዩ ችግሮችን እያነሣ በመካከላቸው ያለውን የመተማመንና የቅን ልቦና ግንኙነት ተጠቅሞ ከአንድ ዓመት በላይ ውሉን ሣይፈፅም የሚቆይበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡

ስለዚህ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ይርጋ ተፈፃሚነት የሚኖረው ገዥ ለሻጭ ማስጠንቀቂያ የሰጠበትን ቀን መነሻ በማድረግና ጊዜውን በማስላት ሣይሆን ሻጭ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን በማያሻማ ሁኔታ ገዥ እንዲያውቀው ያደረገበትን ቀን መነሻ በማድረግ መሆን ይገባዋል፡፡

  1. በሁለተኛ ደረጃ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 የተደነገገው የይርጋ ጊዜ ተፈፃሚነት የሚኖረው በሻጭና በገዥ መካከል የተደረገው ውል የማይፈፀምበት የመጨረሻ ቀን በጥብቅ የተወሰነ ከሆነ በውሉ የተወሰነ የጊዜ ገደብ ካለፈ ከአንድ ዓመት በኋላ ገዥ የውል ይፈፀምልኝ ክስ ማቅረቡን በማስረዳት እንደሆነ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2875 መሠረታዊ መርህና የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 ድንጋጌዎች ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2331ንዑስ አንቀጽ 1 እና 2 ድንጋጌዎች ጋር አጣምሮ በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡
  2. በሶስተኛ ደረጃ የሚነሣው ጥያቄ በዚህ ጉዳይ ተጠቃሽና ተፈፃሚ መሆን ያለበት የይርጋ ሕግ ድንጋጌ የትኛው ነው? የሚለው ነው፡፡ ሻጭ በውሉ መሠረት የመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ለገዥ በማያሻማ ሁኔታ ያሣወቀ መሆኑን ባላስረዳበት ሁኔታ ወይም የሽያጭ ውሉ የሚፈፀምበትን ጥብቅ የጊዜ ገደብ ባልተገለፀበት ሁኔታ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 የተደነገገው የአንድ ዓመት የይርጋ የጊዜ ገደብ ተፈፃሚነት የለውም፡፡ በልዩ የሕግ ድንጋጌ የተቀመጠዉ የይርጋ ጊዜ ገደብ ተፈፃሚነት በማይኖረው ጊዜ ወይም በልዩ ሁኔታ የተደነገገ የይርጋ የጊዜ ገደብ ከሌለ ውል ይፈፀምልኝ በሚል መነሻ የሚቀርቡ ክርክሮች ላይ ተፈፃሚት ያለው የይርጋ ሕግ ድንጋጌ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1845እንደሆነ ይህንን ድንጋጌ ይዘት በመመርመር ለመረዳት ይቻላል፡፡

ሰ/መ/ቁ. 38935 ቅጽ 8[13]

ሻጭ የውል ይፍረስልኝ ክስ ለፍርድ ቤት ማቅረቡ ውሉን ለመፈፀም ፍላጎት የሌለው መሆኑን ለገዢ በማያሻማ መንገድ ከማሣወቅ ያለፈ ምክንያትና ውጤት ያለው ተግባር ነው፡፡ ሻጭ ውሉ እንዲፈርስ ሲጠይቅ ውሉ ሕጋዊ በሆነ መንገድ ለማቋቋም የማያስችሉ ጉድለቶች ያሉበት በሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች እንደ ሕግ ሆኖ ሊገዙበት የማይገባ መሆኑን የሚያሣዩ የውሉን ሕልውና ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባና የውል ሕጋዊነት በፍርድ ቤት ተመርምሮ ፈራሽ እንዲባል ወይም እንዲሠረዝ የሚቀርብ ነው፡፡ የውሉ ሕጋዊነትና ሕልውና ጥያቄ ተነስቶበት በፍርድ ቤት በሚመረመርበት ጊዜ ሂደት ገዢ ውሉ ሕጋዊ መሆኑን ከማሣየትና ከማስረዳት አልፎ ውሉ በግዳጅ እንዲፈጽምለት የመጠየቅ ግዴታ አይኖርበትም፡፡

ከዚህ አንፃር ውሉ በፍርድ ቤት ፈራሽ እንዲሆን ወይም እንዲሰረዝለት በውሉ የሚገደድበት ሁኔታ ይቋረጣል፡፡ በሌላ በኩል በክርክሩ ከተረታ ገዢ ሕጋዊ ተፈፃሚነትና አስገዳጅነት ባለው ውሉ ንብረቱን የገዛ መሆኑ ከሻጭ ጋር ባደረገው የውል ሰነድ ብቻ ሣይሆን በፍርድ ቤት ውሣኔ የተረጋገጠለት የፍርድ ባለመብት ይሆናል፡፡ ስለሆነም ገዢ ፍርድ ቤቱ ሕጋዊነቱንና አስገዳጅነቱን መርምሮ በፍርድ ያረጋገጠውን ውል እንዲፈጽምለት ሻጭን የመጠየቅ መብቱ በፍርድ ከተረጋገጠበት ጊዜ ጀምሮ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 384/ሀ/ በተደነገገው አስር ዓመት ጊዜ ውስጥ እንጂ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀጽ 3 በተደነገገው የአንድ ዓመት የጊዜ ገደብ የሚገደብ አይደለም፡፡ ስለዚህ የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2892 ንዑስ አንቀስ 3 የተቀመጠው የጊዜ ገደብ በዚህ ጉዳይ አግባብነት የለውም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 39725 ቅጽ 8[14]

ይርጋ መነሻ ጊዜ(የ—)

ይርጋ መቆጠር የሚጀምርበት ጊዜ

የይርጋ ቀን መቆጠር የሚጀምረው ግዴታውን ለመጠየቅ ተገቢ ከሆነው ወይም ውሉ የሚሰጠው መብት ከተሰራበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡

የሥራ ውል የተቋረጠበትና የስንብት ደብዳቤ የተሰጠበት ቀን ከተለያየ ይርጋ መቆጠር የሚጀምረው ደብዳቤው ለሠራተኛው ከተሰጠበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 94931 ቅጽ 16፣[15] ፍ/ብ/ህ/ቁ. 1846

በፍትሐ ብሔር ስነ-ስርዓት ህጉ የሚገኙት የጊዜ ገደቦች አቆጣጠር የሚመራው በፍትሐ ብሔር ህግ ባሉት የጊዜ አቆጣጠር ደንቦች ነው፡፡

ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ ውሳኔ የተሰጠበት ወገን ውሳኔው እንዲነሳለት በፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 78/1/ መሰረት በአንድ ወር ውስጥ የሚያቀርበው ጥያቄ የአንድ ወር ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው ውሳኔ መሰጠቱን ከተረዳበት ቀን ጀምሮ ነው፡፡ ሆኖም የመጀመሪያው ቀን ለይርጋው ጊዜ መቆጠር መነሻ አይሆንም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 76601 ቅጽ 13፣[16] ፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 78/1/

በወራሾች መካከል ውርስ እንዲጣራ አቤቱታ መቅረብ ያለበት በሶስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሲሆን ይህም ጊዜ መቆጠር የሚጀምረው አንደኛው ወራሽ የውርሱን ንብረት በእጁ ካደረገበት እንጂ ስመ ሀብቱን በስሙ ካዞረበት ጊዜ ጀምሮ አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 52407 ቅጽ 11፣[17] ፍ/ህ/ቁ. 1000/1/

ከውርስ ሃብት ጋር በተያያዘ ወራሽ የሆነና አካለ መጠን ያልደረሰ ሰው ላይ የይርጋ ጊዜ ሊቆጠር የሚገባው አካለ መጠን ከደረሰበት ጊዜ አንስቶ ነው፡፡

ሰ/መ/ቁ. 57114 ቅጽ 11[18]

ይዞታን አስመልክቶ ከሚነሳ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ ጋር በተያያዘ ተፈፃሚ የሚሆነው የይርጋ ጊዜ መቆጠር ያለበት አቤቱታ አቅራቢው የይዞታ መብቱን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ከሚመለከተው አካል ካገኘበት ቀን ጀምሮ እንጂ አቤቱታ የቀረበበት ድርጊት መፈፀም ከጀመረበት ዕለት አይደለም፡፡

ሰ/መ/ቁ. 60392 ቅጽ 11፣[19] ፍ/ብ/ህ/ቁ. 1140፣ 1149፣ 1146/1/፣ 1144/2/

[1] አመልካች አቶ አብደራዛቅ ሀሚድ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጥቅምት 05 ቀን 2002 ዓ.ም.

[2] አመልካች አንበሳ ኢንሹራንስ ኩባንያ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጥር 05 ቀን 2007 ዓ.ም.

[3] አመልካች አቶ አብደራዛቅ ሐሚድ እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጥቅምት 05 ቀን 2002 ዓ.ም.

[4] አመልካች አሊ ቃሌብ አህመድ እና ተጠሪ እነ አቶ ሚሊዮን ተፈራ /3 ሰዎች/ መጋቢት 18 ቀን 1999 ዓ.ም.

[5] አመልካች ወ/ሮ ድንቄ ተድላ እና ተጠሪ እነ አቶ አባተ ጫኔ መጋቢት 20 ቀን 1999 ዓ.ም.

[6] አመልካች የኪራይ ቤቶች አስተዳደር ድርጅት እና መልስ ሰጪ ሚ/ር ቢሮኒ አቲክፖ ሐምሌ 19 ቀን 1997 ዓ.ም.

[7] አመልካች የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግንቦት 12 ቀን 2000 ዓ.ም.

[8] አመልካች የኢትዮጵያ መድን ድርጅት እና ተጠሪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግንቦት 12 ቀን 2000 ዓ.ም.

[9] አመልካቾች እነ ወ/ሮ አለዊያ ዑመር /7 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ሐሺም ሁሴን የካቲት 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

[10] አመልካች የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይሌ ኮርፕሬሽን እና ተጠሪ አቶ አማረ ገላው ሀምሌ 30 ቀን 2002 ዓ.ም.

[11] አመልካች እነ አቶ ይሌማ አንበሴ /4 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ እመቤት መንገሻ /5 ሰዎች/ መጋቢት 6 ቀን 2002 ዓ.ም.

[12] አመልካች ወ/ሮ አሌማዝ ተሰማ እና ተጠሪ እነ አቶ በየነ ወ/ሚካኤሌ/2 ሰዎች/ መጋቢት 22 ቀን 2002 ዓ.ም.

[13] አመልካች እነ አቶ ወልደፃድቅ ብርሃኑ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ስንታየሁ አያሌው መጋቢት 3 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.

[14] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ዓለምሸት ካሣሁን /3 ሰዎች/ እና ተጠሪ አቶ ሽመልስ እንዳለ ሐምሌ 23 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም.

[15] አመልካች ወ/ሮ ጥሩወርቅ መንግስቴ ተጠሪ የተገጣጣሚ ህንፃ አካላት ማምረቻ ድርጅት የካቲት 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

[16] አመልካች አቶ ሽመልሽ አማረ እና ተጠሪ አቶ አማረ መኮነን ሰኔ 18 ቀን 2004 ዓ.ም.

[17] አመልካቾች እነ ወ/ሮ ውልታ ደስታ ወ/ማሪያም /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ ወ/ሮ እቴቴ ደስታ ኅዳር 27 ቀን 2003 ዓ.ም.

[18] አመልካች ወ/ሮ ሃና ፀጋዬ እና ተጠሪ ወ/ት ጣዕሙ ደስታ ግንቦት 3 ቀን 2003 ዓ.ም.

[19] አመልካች አቶ ጌትነት የኔው እና ተጠሪ አቶ ኢዩብ ቢንያም ወ/ቢኒያም ታህሣሥ 26 ቀን 2003 ዓ.ም.


Filed under: Articles, Case Comment

Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

Trending Articles