Quantcast
Channel: Articles
Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

የጠ/ሚኒስቴር ጽ/ቤት፡ የስልጣን ምንጭ እና ህጋዊነት

$
0
0

ከ10 ዓመት በላይ ማንሳትና መጣል በኋላ ‘የአስተዳደር ህግ መግቢያ’ የሚለው መጽሀፌ እነሆ 2010 ላይ ሲጠናቀቅ ትልቅ እፎይታ ተሰምቶኛል፡፡ የህትመት ነገር ከተሳካ በቅርቡ ገበያ ላይ ይውላል፡፡ የሚከተለው ጽሁፍ የተወሰደው ከመጽሐፉ ረቂቅ ላይ ነው፡፡

የጠ/ሚኒስቴር ጽ/ቤት፡ የስልጣን ምንጭ እና ህጋዊነት

በተለምዶ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት (አንዳንዴ ቢሮ) እየተባለ የሚታወቀው አካል ስልጣንና ተግባሩ በህግ ተወስኖ አልተቋቋመም፡፡ በአቋሙ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የግል ቢሮ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በህገ መንግስቱ የተሰጡትን ስልጣንና ተግባራት በአግባቡ እንዲያከናውን ለማገዝ የሚረዱ የቢሮ ስራዎችን ከማከናወን በስተቀር በማናቸውም መንግስታዊ ሆነ አስተዳደራዊ ጉዳዮች የመወሰን ሆነ ለበታች አካላት መመሪያ የማስተላለፍ ስልጣን የለውም፡፡

ጽ/ቤቱ በታሪካዊ አቋሙ ከነበረው የቆየ ስም እንዲሁም የደርግ መውደቅን ተከትሎ በሽግግሩ መንግስት ጊዜ በዘልማድ በሚያከናውናቸው መንግስታዊ ተግባራት (በተለይ ቅሬታ ሰሚ በመሆን) የተነሳ በህግ ሳይሆን በዕውቅና (de facto) ህልውና ያገኘ የመንግስት ተቋም ለመሆን በቅቷል፡፡

በሰ/መ/ቁ. 16195[1] ተጠሪዎች በመንግስት ለተወረሱ መኖሪያ ቤቶቻቸው አበል እንዲከፈላቸው የሥራና ከተማ ልማት ሚ/ር በወሰነላቸው መሰረት ይከፈላቸው ዘንድ በአመልካች ላይ ክስ አቀረቡ፡፡ ከክርክሩ በኋላ ክሱ እስከቀረበበት ጊዜ ድረስ ያለው አበል እንዲከፈላቸው ተፈረደላቸው፡፡ ፍርዱም በከፍተኛው ፍ/ቤት ፀና፡፡ ሆኖም የሰበር ችሎት ሻረው፡፡ በመዝገቡ ላይ የሥራና ከተማ ልማት ሚ/ር ውሳኔ በጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ እንደተሻረ ተመልክቷል፡፡ በዚህ መልክ መሻሩ ለስር ፍ/ቤቶችን ውሳኔ ለመሻር ምክንያት ሆኗል፡፡ ችሎቱ ህገ መንግስቱን በማጣቀስ ለማብራራት እንደሞከረው፤

[በኢ.ፌ.ዲ.ሪ.] ህገ-መንግስት አንቀጽ 74/4/ ሁሉም ሚኒስቴሮች የሚገኙበትን የሚኒስቴሮች ምክር ቤት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚመራ፣ እንደሚያስተባብርና እንደሚወክል ተመልክቷል፡፡ እንዲሁም…የአስፈፃሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው አ/ቁ 4/87 አንቀጽ 11/1/ ሥር እያንዳንዱ ሚኒስትር፣ የሚመራውን ሚኒስቴር መ/ቤት የሚመለከቱ ሥራዎች ፕሮግራሞችና ህጎች አፈፃፀም ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩና ለሚኒስቴሮች ምክር ቤት መሆኑ ተገልጿል፡፡ ከነዚህ ህጎች አኳያ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚኒስቴር መ/ቤቶችን በበላይነት የመምራትና ስራቸውንም የመቆጣጠር ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡ በመሆኑም ሚኒስቴር መ/ቤቶቹ ሥራቸውን በሚያከናውኑበት ወቅት የፈፀሙትን ስህተት ማረምና ማስተካከል በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ስር የሚወድቅ ነው፡፡

የሥራና ከተማ ልማት ሚ/ር ውሳኔን የሻረው ጽ/ቤቱ እንጂ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አይደለም፡፡ ሆኖም የሰበር ችሎት የውሳኔውን ህጋዊነት ያጣራው የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህገ መንግስታዊ ስልጣን በማመሳከር ነው፡፡ ሁለቱ እንደ አንድ አምሳል፣ አንድ አካል ተቆጥረዋል፡፡ ይህ የማደባላለቅ ስህተት በሌሎች የህግ ባለሞያዎች ላይም ይታይል፡፡ በቅርቡ የጠቅላይ ዓቃቤ ባጠናቀረው የተጠቃለሉ ህጎች ማውጫ ላይ ‘ለጠ/ሚኒስቴር ጽህፈት ቤት ተጠሪ የሆኑ አስፈጻሚ አካላትን ማቋቋሚያ ህጎች’ የሚል ርዕስ እናገኛለን፡፡

ከላይ ለመጠቆም እንደተሞከረው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የሀገሪቱ ርዕሰ መስተዳድር የግል ቢሮ ነው፡፡ የግል የሆነበት ምክንያት እንደ አገሪቱ ፕሬዚዳንት ጽ/ቤት በህግ አልተቋቋመም፡፡ የፕሬዚዳንቱ ጽ/ቤት ማቋቋሚያ አዋጅ ቁ. 131/1991 ጽ/ቤቱን ህጋዊ ሰውነት አላብሶ አቋቁሞታል፡፡ ለጠ/ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ግን ተመሳሳይ የህግ መሰረት የለም፡፡ በስልጣኑ ላይ የሚነሳው ህጋዊና ህገ መንግስታዊ ጥያቄ የማቋቋሚያ አዋጅ አለመኖር ብቻ አይደለም፡፡ ከጊዜ በኋላ ጽ/ቤቱን የሚያቋቁም አዋጅ ቢወጣም እንኳን ከጽህፈት ስራ የዘለለ በማናቸውም መንግስታዊ ጉዳዮች ውሳኔ የማስተላለፍ ሚናና ተግባር ሊኖረው አይችልም፡፡

የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ከህገ መንግስቱ የሚመነጩት ስልጣናት ከእርሱ በቀር ወደ ሌላ አይተላለፉም፡፡ ከምክትል ጠ/ሚኒስትሩ በቀር ሚስት/ባል፣ ልጅ፣ ወላጅ፣ ጽ/ቤት ሆነ ሌላ ማናቸውም አካል የጠቅላይ ሚኒስትሩን ስልጣን መጋራት አልተፈቀደላቸውም፡፡ በህግ የተቋቋመ የሚኒስቴር መ/ቤት የሰጠውን ውሳኔ ጽ/ቤቱ መሻር ይችላል ማለት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጅ ተመሳሳይ የመሻር ስልጣን አለው የማለት ያክል ነው፡፡

የሰበር ችሎት ይህን ግዙፍ ህገ መንግስታዊ ስህተት በሰ/መ/ቁ. 34665[2] ላይም ደግሞታል፡፡ በመዝገቡ ላይ የተነሳው የህግ ጥያቄ የባለቤትነት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት (ደብተር) የመሰረዝ ስልጣን ህጋዊነት ሲሆን የፍሬ ነገሩ መነሻ ታሪክ አስደማሚና አስገራሚ ነው፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በወቅቱ ማለትም በ1991 ዓ.ም. ላይ የስራና ከተማ ልማት ሚ/ር በመስሪያ ቤቱ ይገኙ የነበሩ የቤት ጉዳዮችን ከሰራተኞቹ ጋር ለአዲስ አበባ መስተዲድር ምክር ቤት ስራና ከተማ ልማት ቢሮ እንዲያስረክብ ከጠቅላይ ሚ/ር ጽ/ቤት ትእዛዝ ደረሰው፡፡ በትዕዛዙ መሰረት ሚኒስቴር መ/ቤቱ ጉዳዮቹንና ሰራተኞቹን አስረከበ፡፡ የአ/አበባ መስተዳድ ቤት ስራና ከተማ ልማት ቢሮ ከየካቲት 1 ቀን 1991 ዓ.ም ጀምሮ የቤት ጉዳዮቹን ተረክቦ ማስተዳደር ጀመረ፡፡ ቢሮው በዚህ ሁኔታ የአመልካቾችን ባለቤትነት ማረጋገጫ ደብተር በመሰረዙ ምክንያት በስር ፍ/ቤት ክስ አቅርበው ጥያቄያቸው ተቀባይነት አጣ፡፡ ይግባኝ ቢሉም አቤቱታቸው ውደቅ በመደረጉ ጉዳዩ ወደ ሰበር ችሎት አመራ፡፡ አመልካቾች በሰበር ክርክራቸው ደብተሩ ስልጣን በሌለው አካል እንደተሰረዘ በመጥቀስ የቢሮውን ተግባር ህጋዊነት ሞግተዋል፡፡

በህግ የተቋቋ የመንግስት መ/ቤት ስልጣን፣ መብትና ግዴታ ወደ ሌላ የሚተላለፈው ህግ አውጭው አምኖበት በአዋጅ ሲያጸድቀው ብቻ ነው፡፡ አንድ መ/ቤት በበላይ ትዕዛዝ (ያውም በጠ/ሚኒስትር ጽ/ቤት) የሚበተን ከሆነ፣ ስልጣኑን ተቀምቶ ወደ ሌላ የሚተላለፍ ከሆነ ያኔ ህጋዊነትና ስርዓት አልበኝነት አንድ ሆነው ተዋህደዋል፡፡ የሰበር ችሎት ይህ አስደንጋጭ እውነት  አልተገለጠለትም፡፡ የስር ፍ/ቤቶችን ውሳኔ ሲያጸና በሰ/መ/ቁ. 16195 ያሰፈረውን (የተሳሳተ) ትንተና በመድገም ነገሩን በአጭሩ ቋጭቶታል፡፡ በሰ/መ/ቁ. 34665 የተለየ ነጥብ የሚስተዋለው ጠቅላይ ሚኒስትሩና ጽ/ቤቱ ቦታ ተቀያይረዋል፡፡ ለንፅፅር ይረዳ ዘንድ ሙሉ ዓረፍተ ነገሩ እንደሚከተለው ይነበባል፡፡

የጠቅላይ ሚ/ጽ/ቤት የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ስራ የመከታተልና በበላይነት የመቆጣጠር ስልጣን ያለው እንደመሆኑ መጠን የስራና ከተማ ልማት ሚ/ር ቤቶችን የሚመለከት ጉዳይ ለአ/አበባ ስራና ከተማ ልማት ቢሮ እንዲያስተላልፍ በተሰጠው ትእዛዝ መሰረት ስራውንና ሰራተኞቹን ለቢሮው አስተላልፏል፡፡ (ሰረዝ የተጨመረ)

 

[1] አመልካች የኪራይ ቤቶች ድርጅት እና ተጠሪ እነ ልዕልት ተናኘወርቅ ኃ/ስላሴ /6 ሰዎች/ ቅጽ 4 ሚያዝያ 11 ቀን 1999 ዓ.ም.

[2] አመልካች እነ አቶ ናትናኤሌ ዘውገ /2 ሰዎች/ እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ እግዜሩ ገ/ሕይወት /2 ሰዎች/ ሰ/መ/ቁ. 34665 ቅጽ 10 ጥቅምት 12 ቀን 2002 ዓ.ም


Filed under: Articles

Viewing all articles
Browse latest Browse all 139

Trending Articles